ግምገማ

ሰውዬው ስልጣኑን በመጠቀም በድርጅቱ ውስጥ የሰራውን ሃጢአት እየተናገረ
ሂስ እያወረደ ነው አሉ በፓርቲው አባላት።
"አራት የመንግስት መኪናዎችን በአራቱ ልጆቼ ስም አዘዋውርያለው።"
"እሺ ቀጥል!" ቃለ ጉባዔ እየተያዘ ነው።
"በስሜ ሰባት መቶ ሄክታር መሬት ወጣ ብላ ከምትገኘው የገጠር ከተማ
ወስጃለው።"
"ቀጥል!"
"በሚስቴም ያን ያህል ነው ባይባልም ሁለት መቶ ሃምሳ ሄክታር መሬት ወስጃለው።"
"ሌሎች ተረኞች ስላሉ ፈጠን ፈጠን እያደረክ ቀጥል።"
"በእንጀራ ልጄም ስም እዚሁ ከተማ አንዲት አነስተኛ ባለ ሶስት የቀበሌ ቤት
ወስጃለው።"
"ቀጥል!"
"በሚስቴ ወንድም ስምም እንዲሁ ከመንገድ ዳር ስምንት መቶ ሃምሳ ካሬ ሜትር መሬት ወስጃለው"
"ሌላስ ቀጥል!"
"በሚስቴ እህት ስም ሁልት ተሳቢ መኪና ከ አንድ የአጎቴ መስሪያቤት በጨረታ
ገዝቻለው"
"ቀጥል!"
ቃለ ጉባዔ የሚይዘው ፀሃፊ አንገቱን ወደ ባሕረ መዝገቡ ደፍቶ እጁን እስኪደክመው እየፃፈ ነው።
ከዘንድሮው የኑሮ ውድነትና ከድህነቱም በላይ ለታላቅ ጉስቁልና የዳረገው በእንዲህ ዓይነቱ ጉባዔ ላይ
የሚፅፋቸው ኑዛዜዎች ናቸው።
"ከተማው ውስጥም ለጤና ጣቢያ መስሪያ የተያዘ በቅርቡ የመሰረት ድንጋይ
የተቀመጠበት መሬት በራሴ ወንድም ስም ወስጄ ፑል ቤቶችን ከፍቻለሁ"
"እሺ ቀጥል!"
"በቃ ከዚህ በላይ ምንም አልወሰድኩም"
"እንደው ምንም!?"
"ምን ማለታችሁ ነው? ትንሽ አስቡልኝ እንጂ!ከዚህ በላይ ዘመድ ከየት አመጣለሁ!?"
*ኑሮ እና ፖለቲካ በኃይሉ ገ/እግዚአብሔር ገፅ-54-55

posted by Ethiounited Moderator at3:49 PM

0 Comments:

Post a Comment

<< Home