“መለስ ስለሞቱ የስዬ ጎራዴ ወደ አፎቱ ”

አዜብ ጌታቸው
አቶ ስዬ አብርሃ በአቶ መለስ የቦናፓርቲዝም ስሌትና ማጣፋት ህይወታቸውን ለመስጠት ከቆሙለት ድርጅት መባረራቸው ሳይበቃ 6 ዓመታትን በዘብጥያ አሳልፈዋል፡፡ በኔ እምነት የአቶ መለስ አይራሬነትና ጭካኔ ከተገለጠባቸው በርካታ ውሳኔና እርምጃዎቻቸው አንዱና ዋንኛው ይህ በአብሮ አደግ ጓደኞቻቸው ላይ የወሰዱት ምህረት የለሽ እርምጃ ነው።
በወቅቱ በአቶ ስዬና ጓደኞቻቸው ላይ በደረሰው ነገር አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ማዘኑን አስታውሳለሁ። በተለይ እነ አቶ ስዬን ለዚህ ያበቃቸው በኤርትራ ላይ ከአቶ መለስ ጋር የነበራቸው ልዩነት እንደሆነ ከታወቀ በኋላ የአቶ ስዬ ቡድን ተሸናፊ መሆኑ ኢትዮጵያዊውን ሁሉ አስቆጭቶ ነበር። ይህ ሁሉ አልፎ አቶ ስዬ 6 ዓመታትን በእስር ማቀው በመጨረሻም ነጻ ወጡ ተብሎ ሲለቀቁም ተደስተናል። የታሰሩት ትዕቢተኛው ስዬ እንደነበሩና የተፈቱት ግን የሰከነው ስዬ እንደነበሩም ትዝ ይለኛል። አቶ ስዬ ከእስር ከወጡ በኋላ እንደ ሌሎቹ ጓደኞቻቸው ጎመን በጤና ብለው መቀመጥን ሳይመርጡ ወደ ትግሉ ጎራ መቀላቀላቸውም በመታሰራቸው ያዘነውን ኢትዮጵያዊ አስደስቷል። የበለጠ ያስደሰተው ደግሞ ከአረና ትግራይ ይልቅ አንድነትን መቀላቀላቸው ነበር።በግዜው እኔም ይህንኑ ውሳኔያቸውን አወድሼ መጻፌን አስታውሳለሁ።
ይሁን እንጂ አቶ ስዬ አንድነትን ከተቀላቀሉ ብዙም ሳይቆዩ ነበር አካላቸው እንጂ አንድነትን የተቀላቀለው ልባቸው እዛው ህውሃት ውስጥ እንደነበር ያመላከተ አቋማቸውን የገለጹት። ቢቢሲ የዘገበውን ዶ/ር አረጋዊና አቶ ገብረመድህን አርአያ ሙሉ ለሙሉ ያረጋገጡትን ወ/ሮ አረጋሽ በከፊል ያመኑትን ለረሃብተኛ የመጣ እህል ዘረፋ አቶ ስዬ ሽምጥጥ አድርገው መካዳቸውን ያስታዉሷል።
•የአቶ ስዬ የተልፈሰፈሰ የሰላማዊ ትግል ፍልስፍናም ቀልባቸው ከአንድነቱ ጎራ አለመሆኑን ያሳየ ሌላው ምዕራፍ ነበር፡፡
•አቶ ስዬ ህዝባዊ አመጽ የሚለውን የሰላማዊ ትግል ዋናና ውጤታማ ስልት አጥብቀው ይቃወማሉ፡፡
•አቶ ስዬ መከላከያ ሰራዊቱን በመንግስት ላይ እንዲነሳ መቀስቀስ ህገ መንግስቱን መጣስ ነው ብለው ይሞግታሉ፡፡
•አቶ ስዬ የወያኔ ጀነራሎችንም ልናቅፋቸው ይገባል ሲሉ ይሰብካሉ።
 ልብ በሉ አቶ ስዬ ለእርዳታ የመጣ እህል አልሸጥንም ብለው በመመስከር ህውሃት እንዲነካባቸው አለመፈለጋቸውን አረጋግጠውልናል። መከላከያ ሰራዊቱ በመንግስት ላይ እንዲነሳ መቀስቀስ ህገ መንግስት መጣስ ነው ብለው በትግራይ የበላይነት የሚመራውን መንግስት ውድቀት እንደማይሹ ገልጸውልናል። ጀነራሎቹን ልናቅፋቸው ይገባል ብለው ጓደኞቻቸው እንዳይነኩ ሰብከውናል።
እንግዲህ አቶ ስዬና መሰረታዊ ለውጥ ፈላጊው ወገን የጋራ ጠላት ሊሆን የሚችል ማን ቀረ ? ብለን ጥቂት ጣራ ጣራ እያየን ብንቆይ …መለስ ዜናዊ የሚለው ስም ግልጽ ብሎ ሊታየን ግድ ነው። ምክንያቱም መከላከያ ሰራዊቱን ከነጀነራሎቹ እንዲነካ ካልፈለጉ፤ ህገ መንግስቱ እንዲከበር ከፈልጉ፤ የድሮ ድርጅታቸው ስም እንዳይጠፋ ከፈለጉ፤ አቶ ስዬ የማይፈልጉት አቶ መለስን ብቻ ነው ማለት ነው።
ይህ በእንዲህ ቀጥሎ ቆይቶ፣ ሰው ያስባል ጌታ ይፈጽማል ሆነና በቅርቡ የአቶ ስዬና የሌላው ተቃዋሚ ወገን የጋራ ባላጋራ የነበሩት መለስ ዜናዊ ባልተጠበቀ ሁኔታ ተመልሰው ወደ ማይመጡበት አለም መሄዳቸው እውነት ሆነ። ይህ ማለት ደግሞ የአቶ ስዬ የትግል ጉዞ ተቋጨ ማለት ነው። በሌላ አገላለጽ ” መለስ ስለሞቱ የስዬ ጎራዴ ወደ አፎቱ”መሆኑ ነው።
ሰሞኑን ያረጋገጡልንም ይህንኑ ነው። አቶ ስዬ ጭራሽ በአቶ መለስ ሞት ተደስተናል ያሉ ወገኖችን ኢትዮጵያዊ ጨዋነታችንን ያልተከተለ አስነዋሪ ተግባር ፈጽመዋል ሲሉ ወቅሰዋል። አቶ ስዬ እነኚህ ወገኖች ምንም እንኳ ጥቂት ቢሆኑም ጥላቻን በማዛመት ከፍተኛ ጥፋት ሊያደርሱ ይችላሉ በማለት ወቀሳና ስጋት የቀላቀለ አስተያየት ሰጥተዋል።
እንዲያው አቶ ስዬን ልጠይቅ የምሻው ለመሆኑ ኢትዮጵያዊ ጨዋነትን ፤ ባፍጢሙ የደፋው ማነውና ነው ዛሬ ያገርዎ ልጅ ለዛውም በጠላትነት የፈረጁት ሰው ሲሞት ተደስተናል ያሉ ወገኖችን ወቃሽ የሆኑት?
ለመሆኑ ፕሮፌሰር መስፍንን የሚያህል በሺህ የሚቆጠር ዜጋ ያነጹ ውድና የሃገር ቅርስ የሆኑ የ76 አመት አዛውንት በማንም ውርጋጥ በሰደፍ እየተመቱ ዘብጥያ የተጣሉት ኢትዮጵያዊ ጨዋነታችን ፈቅዶት ይሆን?
ለመሆኑ በሞተው ወንድሙ ሬሳ ላይ ተንበርክኮ የሚያለቅስን ህጻን በጥይት በሳስቶ በሬሳ ላይ ሬሳ መደራረብ ኢትዮጵያዊ ባህል ነበርን?
ለመሆኑ ወራዳ ! ጨምላቃ! የበሰበሰ! ….የሚሉት አስነዋሪ ቃሎች በማን ይዘወተሩ እንደ ነበር ኢትዮጵያዊ ጨዋነታችን ተናደ ብለው የተቆጩት አቶ ስዪ ያስታውሱ ይሆን? እረ ስንቱን ልጥቀስ….
እናም አቶ ስዬ ሆይ! ከላይ የጠቃቀስኩዋቸው የባህል ጥሰቶች ብቻም ሳይሆኑ ግፎች ሲፈጸሙ የት ነበሩ? ያኔ ቃል ያልተነፈሱት ዛሬ በጭካኔ በትራቸው እርስዎንም ሳይቀር በዠለጡት መለስ ዜናዊ ሞት በተሳለቁ ሰዎች ማዘንዎ ከተለከፉበት የዘረኝነት በሽታ የመነጨ እንጂ ሌላ ምን ሊሆን ይችላል እንበል?
አቶ ስዬ በቅርቡ በሲያትል ባደረጉት ንግግር ግልጽ ያደረጉት ዋናው ነገር ከእንግዲህ በሰላማዊም ይሁን በትጥቅ ትግል የህውሃትን መንግስት ከስሩ ነቅሎ ለመጣል ከሚታገለው ወገን ጋር ምንም የጋራ ነገር እንደሌላቸው ነው፡፡
•አቶ ስዬ በንግግራቸው ለ21 ዓመት የነበረውን ሰላም እንዲቀጥል ሲሉ ተደምጠዋል። በአቶ ስዬ አባባል ጦርነት እስከሌለ ድረስ ሁሉ ነገር ሰላም ነው።
•በአቶ ስዬ አባባል ጦርነት እስከሌለ ድረስ ዜጎች ያለጥፋታቸው ለዘመናት በእስር መማቀቃቸው ኢሃዴግ ታግሎ ያመጣው ሰላማዊ እስር በመሆኑ ወደፊትም መቀጠል አለበት።
•አቶ ስዬ የሚሉን የባሩድ ጭስ ሰማዩን እስካልሸፈነ ድረስ ሰላማዊ ሰልፍ የወጡ ዜጎችን መረሸን ከሰላም ጋር ምንም ግንኙነት የለውም። ገዳዮቹም ሰላማዊ ገዳዮች ሟቾቹም ሰላማዊ ሟቾች ናቸው።
•አቶ ስዬ እንደሚያስረዱን ባዙቃ እስካልተንተከተከ ድረስ 80 ሚሊዮኑን ህዝብ ለድህነትና ለርሃብ አጋልጦ የአንድ ዘር ውላጅ የሆነው አናሳ ክፍል በዘረፋና በምዝበራ ሃብት መሰብሰቡ ሰላማዊ ምዝበራ ስለሆነ እንደነበር እንዲቀጥል መታገል አለብን።
ቃል በቃል ባይሆንም አቶ ስዬ ህዝቡ ንብረቱን ማጣት ስለማይፈልግ መረጋጋትና ሰላም ይፈልጋል አይነት መልዕክት ያለው ነገር ተናግረዋል፡፡
እንደኔ ግምት አቶ ስዬ ህዝቡ ሲሉ የትግራይን ሕዝብ ማለታቸው ነው፡፡ ምክንያቱም በመጀመሪያ ደረጃ ንብረቴን እንዳላጣ ብሎ ሊሰጋ የሚችለው ንብረት ያለው ህዝብ ነው። ስለዚህ ንብረቴን እንዳላጣ ብሎ የሚሰጋው፤ የሚልሰው የሚቀምሰው አጥቶ የሚሰቃየው የኢትዮጵያ ህዝብ ሳይሆን 21 ዓመት ዘርፎና መዝብሮ ንብረት ያከማቸ ህዝብ ነው።
በሲያትሉ ንግግራቸው በከፊል የግብረገብ አስተማሪ በከፊል የባህል ተቆርቋሪ በጨረፍታ ደግሞ የትግል ስትራተጂ ነዳፊ የመሰሉት አቶ ስዬ፤ ሱዛን ራይስን ከመንቀፍ ይልቅ ብንደግፋት ይሻል ነበር በሚል አርቆ አሳቢ ያስመስለኛል ያሉትን ምክር ቢጤም ሰንዝረዋል። በርግጥም ሱዛን ራይስን በመስደብ ወይም በመቃወም የሚገኝ ጥቅም ላይኖር ይችላል፡፤ ይሁንና አቶ ስዬ የሰጡት ምክር የአሜሪካ ባለስልጣናትን ሞገስ ለማግኘት ፈልገው ካልሆነ በስተቀር ሱዛን ራይስን በማወደስም ቢሆን ምንም ጠብ የሚል ነገር እንደሌለ እሳቸውም ያውቁታል እኛም እናውቀዋለን።
በደምላላው አቶ ስዬ ከመለስ በስተቀር ከቀሪው የወያኔ መንግስትና ባልስልጣናት ጋር ምንም አይነት ቅራኔ ስለሌላቸው በሲያትሉ ንግግራቸው ከዚህ በፊት በመጠኑም ቢሆን ያውግዙት የነበረውን የመንግስት ኢዲሞክራሲና ኢሰባዊ ተግባር ከማውገዝ ተቆጥበዋል። ይህ ደግሞ በራሱ የአቶ ስዬ ቀጣዩ እንቅስቃሴ ምንና ወዴት አቅጣጫ እንደሚሆን የሚጠቁም ይመስለኛል።
ሌላው ከአቶ ስዬ የአነጋገር ዘይቤ የተገነዘብኩት እራሳቸውን” ከኛ በላይ ስለ ትግልና ፖለቲካ ላሳር… አይነት እራስን አግዝፎ የማየት ስሜትን ነው። አላወቅሽ ….አሉ!
ባጠቃላይ ከላይ ለመግለጽ እንደሞከርኩት የአቶ ስዬ የተቃዋሚነት ጉዞ በአቶ መለስ ሞት ማግስት ተቋጭታል። አቶ ስዬ ትልቁ ጠላታቸው መለስ ነበሩ። ከእስር በኋላ ወደ ትግል የገቡበት አላማም በቀልን እንጂ የነጻነትና የዲሞክራሲን መከበር ያማከለ አልነበረም፡፤
የአቶ ስዬ 2 ዋና ዋና አላማዎች፦
 1. ኛና ቀዳሚው አላማ መለስን ስልጣኑን አሳጥቶ መበቀል ከተቻለም ስልጣኑን መረከብ ነበር
2. 2ኛው በአንድነት ፓርቲ ውስጥ ግዙፍ ስልጣን ይዞ የትግራይ ተወላጆች ለ21 አመት በዘረፉት ሃብት ያገኙትን የኢኮኖሚ የበላይነት ሳይለቁ እንዲቆዩ ማድረግ ነው።ይህም ደግሞ
 ህዝቡ ንብረቱን እንዳያጣ ስለሚሰጋ ሰላምና መረጋጋት ይፈልጋል ሲሉ አረጋግጠልናል።አቶ ስዬ አንድነት ፓርቲን የተቀላቀሉትም ለዋናው አላማቸው እንደ ስትራተጂ ለመጠቀም እንጂ አንድነትን አላማ አድርገው አለመሆኑን በንግግራቸው ቁልጭ አድርገው አሳይተውናል።
እኛም አውቀናል የዲሞክራሲ ናፋቂው ወገን አላማና የአቶ ስዬ አብርሃ አላማ የመሳ ለመሳ ቅራኔ ያለው መሆኑን ተረድተናል። ዲሞክራሲ ናፋቂው ወገን አቶ መለስ ኖረው መንግስታቸው ቢሞት ይመርጣል።አቶ ስዬ ደግሞ የሚሹት ተቃራኒውን ነው።ስለዚህ ለግዜው አቶ ስዬ ፌርማታቸው ላይ ደርሰው ወርደዋል። ከአሁን በኋላ አቋራጭ መንገድ ፈልገው ወደ ትውልድ ሰፈራቸው መግባት ነው። እኛም እስከ …..እንጓዛለን እንደርሳለንም።

ኢትዮጵያ ለዘላለም በክብር ትኑር
አዜብ ጌታቸው
azebgeta@gmail.com

posted by Ethiounited Moderator at10:02 AM

0 Comments:

Post a Comment

<< Home