ቅንጅት እና አቶ ሀይሉ ሻውል

ከተሰሎንቄ
ኢትዮጵያውያን ሃገራቸውን ከገባችበት ማጥ ለማውጣት በሚያደርጉት የፖለቲካ ትግል እና የፖለቲካ እንቅስቃሴ ድካማቸውን አሳይተው ምስጋና ለማግኘት ሳይሆን ለሃገራቸውና ለራሳቸው የሚመኙት ነፃነት ፣ ፍትሕ ፣ ዲሞክራሲና አንድነት ተወልደው በምድረ-ኢትዮጵያ ለማየት ከመሻት የተነሳ ነው። ለዚህም ነው ከ40 ዓመታት በላይ ገዥውን መደብ የሚታገሉ የሰላም እና የትጥቅ ትግልን መስመር የያዙ የፖለቲካ ድርጅቶችን በእቅፉ ይዞ የትግል ጉዞውን እጅ ለእጅ ተያይዞ ለመጓዝ የተገደደው። ለዚህም ነው ደርግ በጠመንጃ ኃይል ከሠራዊቱ በወጡ መኮንኖቹ የአፄ ሀይለሥላሤን ንጉሳዊ አገዛዝ ሲጥል የሕዝብ እሮሮ እና ጩኸት ረድቶት እና አበረታቶት ቤተ-መንግስቱን ሊወርስ የበቃው፤ እንዲሁም የወያኔ/ኢህአዴግ አምባገነናዊ አገዛዝ በጠመንጃ ኃይል የደርግን አምባገነናዊ አገዛዝ ሙሉ በሙሉ በሆነ የሕዝብ ድጋፍ ገርሰሶ ያው የደገፈውን ሕዝብ ረስቶ፣ ይኅው አሁንም ከቀደምቶቹ ሁለቱ አገዛዞች ባልተናነሰ የሀገሪቱን ሕዝብ ነፃነቱን ነስቶ በአምባገነንት እየገዛ ነው።
ለመሆኑ እንደዚህ አይነቶቹን አምባገነናዊ አገዛዞችን የመታገል መብት ያለው ማን ነው? ወጣም ወረደ ኢትዮጵያውያን ናቸው አምባገነኖችን ታግለው የፈቀዱትንና የመረጡትን እንዲያስተዳድራቸው ለስልጣኑ ብቁ ሊያደርጉት የሚገባው። ይህ ከዚህ በላይ የቀረበው ወግ(principle) ከአለው ተጨባጭ ሁኔታ አንፃር እና ኢትዮጵያ ከአለፈችበት የአገዛዝ ስርዓቶች በጭብጥ ያሳየው የስርዓት ለውጥ ባይኖርም ነገር ግን በሃገራችን ሊጠበቅ የሚገባና በእያንዳንዱ ዜጋ ተከብሮ መቆየት ያለበት ጉዳይ ነው።
ቅንጅት ከ2005 ምርጫ በፊት ለኢትዮጵያ ሕዝብ ከአሰራጨው የፖለቲካ መርሆ መሃል ዋንኛው ዜጋው ራሱን የማስተዳደር ብልሃትን በምርጫ ወቅት በድምፁ የመለወጥ መብት እንዳለው ያለፍርሃት ማሳወቁና ማስተማሩ ነው። ይህ የሕዝብን ምኞት እና መብት የፈሩት አፀፋውን በጥይት እና ብልግና በተሞላው ሁኔታ የሰውን ልጅ ስብዕና ገፈው ስልጣን ጨብጠው ለሁሉም መፍትሔው እኛ ብቻ ነን በሚል ፈሊጥ ላይ ይገኛሉ።
እውነት ቅንጅት የማን ነው? ለምንስ ነው ቅንጅት በኢትዮጵያውያን ልብ ውስጥ ገብቶ እና ሰርፆ መገኘቱ አንዳንዶችን እያደማ የሚገኘው? ምኑ ላይ ነው ጥፋቱ?
መቼም ይህን ፅሁፍ በምፅፍበት ጊዜ የቱን አንስቼ የቱን እንደምጥል አላውቀውም። ነገር ግን ከሁሉ በፊት አስቀዳሚ እና ያሰፈልጋል የምላቸውን እና የማስባቸውን ትህትና በተሞላበት ሁኔታ ላቀርብ እወዳለሁ።
ለአራት ወራት ያህል በቅንጅት መሪ እና በአመራር አባላቶች መካከል የተከሰተው ልዩነት ብዙዎችን ሊያሳዝን ይችላል። ቢሆንም ግን ከእዚህ እውነታ ብዙዎቻችን ተጠቅመናል እንጂ አልተጎዳንም። የተጎዳንባቸው ሁኔታዎች ዛሬ የተፈጠሩ ሳይሆን በቀድሞ ዘመናት በህይወታችን ውስጥ የተከሰቱ እና ክስተታቸው ደግሞ በአስደናቂ ሁኔታ ተመልሰው የመጡብን ናቸው። ወያኔ/ኢህአዴግ የዚህ ክስተት ውጤት ነው። ለወያኔ/ኢህአዴግ በአገራችን ላይ ለሚያደርሰው በደልና ጥፋተኛ አሰራር ትልቅ አስተዋፆኦ ያደረገው “ከኔ በላይ ማን?!” የሚለው ድርቀት ያተሞላበት አመለካከት ነው።
ነገሮች ቢዳፈኑ ምንም ጥቅም የላቸውም። ተዳፍነው ከሰነበቱ ከእንደገና ከተዳፈኑበት ቦታ ሲወጡ መልሰው ጉዳት ማድረሳቸው አይቀሬ ነው። እስከዛሬ ድረስ በዚህ አራት ወራት ውስጥ በቅንጅት ላይ የተፈፀሙትን ደባ ለምስክርነት ደባው ሲፈፀም በቦታው ተገኝቼ ለመስማት እና ለማወቅ በመታደሌ በአንድ መልኩ ሐዘኔ ከፍ ያለ ነበር፡ በሌላ መልኩ በቻልኩበት ቦታ ሁሉ እየተፈፀመ ያለውን ደባ አስፈላጊ በሆነ መልኩ ለማሳወቅ ሞክሬአለሁ።
በቅድሚያ በቅንጅት አለምዓቀፍ አመራር መካከል እና በሻለቃ ዮሴፍ ቡድን በኩል የተደረገው የሽምግልና ሂደት ፈፅሞ እግዚአብሔር በማይወደው መልኩ ዕድሜያቸው ገፋ ባለ ወደ አንድ ወገን ያደሉ እና በውስጣቸው ቂመኝነትንና “የምላችሁን ካልሰማችሁ… ዋ!” በሚሉ አዛውንቶች የተፈፀመ ነው፣ አዝናልሁ።
የቅንጅት አለምዓቀፍ ምክርቤት በሚል መጠሪያ የተሰየመው ድርጅት አመሠራረት በሽምግልና በቅንጅት አለምዓቀፍ አመራር እና በሻለቃ ዮሴፍ ቡድን መካከል ተፈጠረ የተባለውን ስምምነት አስታኮ በመምጣት በባህላችን ታላቅ ቦታ የሚሰጠውን የሽምግልና ልምድ ያቃለለ እና ያዋረደ ነበር። እዚህ ላይ ዱለታው መፈፀም የጀመረው ሁለቱ ታራቂ ቡድኖች ያላቸውን የውስጥ ልዩነት እንኳ ሳይፈቱ ማለትም “ሽማግሌዎች ነን” ብለው የቀረቡት ግለሰቦች ቀድሞውኑ የአንዱ ተሸምጋይ አካል(ወገናዊ) ሆነው እንደቀረቡ አውቅ ነበር። ለማን ልናገረው? ብጮህ ሰሚ አልነበረም፤ አልፈርድም፤ ምክንያቱም እንደእኔ በአካል በተዶለተበት ቦታ ሆኖ ዱለታውን ያየ ባለመኖሩ!!!
በዚያን ወቅት ይህን ሁኔታ ሳዳምጥና ሳስተውል በተለይ የቅንጅት አለምዓቀፍ አመራር አካሎች ሊያዳምጡ ይችላሉ ብዬ በአሰብኩበት ቦታ “እባካችሁን እንዲህ አይነቱ ሽምግልና ውስጥ እንዳትገቡ” የሚለውን መልዕክቴን ላደርስ በሞከርኩ ጊዜ ሽምግልናው በአለምዓቀፉ አመራር በኩል በወቅቱ የታየውንና ያለውን ልዩነት እና ክፍፍል በተቻለ መልኩ ከትግሉ ለማራቅ በሚል እምነት ነው። የሆነ ሆኖ ነገሮቹ እንደፈራሁት ሆኖ በመገኘቱ ያኔ አልተቆጨሁም ነበር። አሁን ግን የዚያን ጊዜ ወይንም ከዚያ በፊት የተፈጠረው ልዩነት ውጤት ይኅው ከምድረ-አሜሪካ አልፎ ከእስር እንዲፈቱ የጮህንላቸው የቅንጅት አመራር አካል ውስጥ ገብቶ የሃገር ቤቱን ትግል እንዲያዘግም እና ዋና ፈሩን እንዲለቅ በማድረጉ ያንገበግበኛል።
በሃገሪቱ እንዲሰፍን የሚፈለገውን የዲሞክራሲ ሂደት በአፅንዖት ለማየት ከአስፈለገ የግድ ትዕግስት የተሞላበት አጠቃላይ የኢትዮጵያን ሁኔታ ማጥናት እና መረዳት ተገቢ ነው። ለዚህ ጉዳይ የግድ የ“ፖለቲካ ሳይንስ” ማጥናት ወይንም “የተማረ” ሆኖ መገኘት ብቻውን ጠቃሚ ሆኖ ሊገኝ አይችልም። እንደዚህ ላለው ትግል በኃይል የመጣን ወይንም ያለውን ፈንግሎ ጥሎ ሌላ ኃይለኛን የኢትዮጵያ ገዢ እንዲሆን መሾሙ በጣም ቀሎ ሊታይ ይችላል። ነገር ግን አሁን ያለው በኢትዮጵያ እየተካሄደ የሚገኘው የትግል አቅጣጫ እያንዳንዳችን ልናገኝ የሚገባንን ነፃነት ላይ ያተኮረ ነው። ማንም፤ ቅንጅቱም ቢሆን፤ ሀገሪቱን ቢመራ የፍትህ፣ የሀሳብ፣ እንዲሁም ድምፅ የመስጠት ነፃነት መከበር ዋንኛው ለሀገራችን ሊኖራት የሚገባና እነዚህ ከላይ የተጠቀሱት ነጥቦች ሀገር አስተዳዳሪዎችና ተዳዳሪዎች የሚመሩባቸው ቁልፍ እሴቶች ሆነው መገኘት ልንታገልበት የሚገባ ነው።
ለምን ይሆን “ቅንጅት ዓለም አቀፍ ምክር ቤት” ብሎ ራሱን የመሰረተው ቡድን ከላይ ከጠቀስናቸው የሕዝብ ራዕይ ውጭ የሆነ አስፀያፊ ተግባር ውስጥ የገባው? እልህ ነውን?! ወይንስ “የበላዩ እኔ ነኝ” በሚል ለራስ የማይገባ ስልጣን ውስጥ መወርወር ነውን?! ዋናው በውስጡ ያቀፈው አካሄድ ለማንም በተለይ በቅንጅት ውስጥ ለታቀፈው አባላት እና ደጋፊ ይበጃል ብሎ ማሰብ የሚፈይደው ምንም ነገር የለም። ይህ ድርጅት የቅንጅትን ማኒፌስቶ ማቀፉ በጣም አጠያያቂ ከመሆኑም ሌላ፡ ህገ-ደንቡ ምን እንደሆነ የማይታወቅ በህቡዕ የሌሎች ድርጅቶች አባሎች እና ደጋፊዎች ከቅንጅት ራዕይ እና ዓላማ ውጭ በሆነ አመለካከት ይዘው በውስጡ እየዋኙበት መሆኑ ነው። ቅንጅት የያዘው ዓላማ ወያኔ/ኢህአዴግ በስልጣን ላይ ኖረም አልኖረ በኢትዮጵያ ላይ ሊሰፍን በሚገባው የነፃነት፤ የመብት፡ እንዲሁም የፍትሕ በሀገሪቱ ውስጥ ተግባራዊ መሆን ላይ ያተኮረ ነው።
በቅንጅት አመራር መሀከል የተፈጠረው ልዩነት በምዕራቡ ዓለም ለሚኖሩ ምሁራን ግልፅ ሆኖ አልታይ ያለበት ምክንያት ምን እንደሆነ ለዚህ ፀሀፊ ግራ ከማጋባቱ ሌላ ምን ያህል እነዚህ ምሁራን በጉዳዩ ላይ ጠለቅ ያለ ምርመራ አለማድረጋቸው በግልፅ እየታየ መሄዱ ነው።
እስቲ ከእስር ከተፈቱበት ጊዜ አንሰቶ የተከሰቱትን ክስተቶች አጠር ባለ ሁኔታ ዘርዘር እያደረግን እንያቸው።
አቶ ሀይሉ ሻውል ከእስር እንደተፈቱ በቀጥታ ወደ አሜሪካ ሄደው ህክምናቸውን ለመከታተል እና እንዲሁም ከቅንጅት ደጋፊዎች ጋር ለመነጋገር ቪዛ ለማግኘት አሜሪካን ኤምባሲ ማመልከቻ ያስገባሉ። በሚያሰገቡበት ወቅት መጀመሪያ ያሰቡት ነገር ቢኖር ከሌሎቹ የቅንጅት አመራር አባላት በቅድሚያ ወደ አሜሪካ ተጉዘው እንዳሰቡት እና እንዳቀዱት ሁሉ ይሳካል ብለው ነበር። እንደዚህ ፀሀፊ ግምት አቶ ሀይሉ ሻውል አስቀድመው ወደ አሜሪካ በመሄድ በግንቦት 1997 ምርጫ ወቅት እንዳደረጉት፤ የገንዝብ ማሰባሰብ እና የሕዝብ-ግንኙነት፤ በምድረ-አሜሪካ ራሳቸው ብቻ ማስፈፀም እና ሀይላቸውን ለማጠናከር እና ለማዳበር ነበር።
ሌላው ደግሞ ከእስር የተፈቱት የቅንጅት አመራር አባሎች በኩል ፀድቆ ከሀገር ውጭ የፖለቲካ ውክልናን በተመለከተ የፖለቲካው ስራ አመራሩ ከእስር እስከተፈታ ድረስ በቅንጅት አመራር በኩል መካሄድ እንደሚጀምር እና በውጭ የሚገኙት በተለይ “ቅንጅት ዓለም አቀፍ ምክር ቤት” እና “ቅንጅት ዓለም አቀፍ አመራር” ስራቸውን እንዲያቆሙ የሚገልፀው መግለጫ በቅንጅት ዓለም አቀፍ አመራር በኩል ተቀባይነት አግኝቶ አመራሩ ሲፈርስ “ቅንጅት ዓለም አቀፍ ምክር ቤት” ግን አልፈረስኩም ብሎ ራሱን ባርኮ መቀመጡ ነው።
አቶ ሀይሉ ሻውል ይህን መግለጫ በፊርማቸው አፅድቀው ነገር ግን ለ“ቅንጅት ዓለም አቀፍ ምክር ቤት” የይገባዋል ስልጣነ-ሹመት ሲሰጡ፡ ይዞ የመጣው መዘዝ ለአቶ ሀይሉ ሻውል መያዣ መጨበጫ ያጣ ከመሆኑም በላይ ለራሳቸውም ሆነ ለድርጅቱ እንደ ሀይሉ ሻውል ሆነው መመሪያ ሊሰጡ አልቻሉም። አቶ ሀይሉ ሻውል በእርግጥ በህመም ላይ ናቸው ቢባል፡ ከዚህም በላይ የሚያዳምጧቸው እና የሚያወያይዋቸው በዚህ ፅሁፍ ውስጥ የጠቀስኩዋቸው የሌላ ፖለቲካ ድርጅት አባሎች እና ደጋፊዎች በዚሁ የቅንጅት የዲሞክራሲ ትግል ውስጥ ገብተው የአቶ ሀይሉ ሻውልን ሕመም እና ሌሎች ገንዘብ ነክ ምክንያቶች አስታከው፤ ይኸው አሁን ቅንጅት የደረሰበት ደረጃ ደርሷል።
..... ይቀጥላል

posted by Ethiounited Moderator at11:26 AM

0 Comments:

Post a Comment

<< Home